በክልሉ ከለውጡ ወዲህ በግብርናው ዘርፍ ያለውን ምቹ አቅም በመጠቀም በተሰሩ ሥራዎች አበረታች ውጤት ተገኝቷል፦ አቶ አሻድሊ ሀሰን ‎*************

በክልሉ ከለውጡ ወዲህ በግብርናው ዘርፍ ያለውን ምቹ አቅም በመጠቀም በተሰሩ ሥራዎች አበረታች ውጤት ተገኝቷል፦ አቶ አሻድሊ ሀሰን
‎*************
‎(አሶሳ፣ ኅዳር 07/2018 ዓ.ም) በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ከለውጡ ወዲህ በግብርናው ዘርፍ ያለውን ምቹ አቅም በመጠቀም በተሰሩ ሥራዎች አበረታች ወጤት መገኘቱን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ አሻድሊ ሀሰን ገለጹ።
‎የክልሉ ግብርና ቢሮ ክልላዊ የ2017/18 የምርት ዘመን የአርሶ አደሮች የመስክ በዓል በባምባሲ ወረዳ አካሂዷል።
‎በወረዳው አያንቱ ቀበሌ በ29 ሺህ 500 ሄክታር መሬት እየለማ የሚገኝ የሊሙ እና 661 የቦቆሎ ዘር ብዜት ክላስተር፣ በቀሽማንዶ ቀበሌ በ59 ሄክታር መሬት ላይ እየለማ የሚገኝ አሶሳ-1 የማሽላ ዘር ብዜት እንዲሁም በመንደር 40 ቀበሌ በ40 ሄክታር ላይ እየለማ የሚገኝ የሩዝ ማሣዎችን ምልከታ ተደርጓል።
‎በመርሃ-ግብሩ የተገኙት የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ አሻድሊ ሀሰን፣ ለውጡን ተከትሎ በክልሉ በግብርናው ዘርፍ ያለውን ምቹ አቅም በመጠቀም በተሰሩ ሥራዎች አበረታች ውጤት መገኘቱን ተናግረዋል።
‎በክልሉ የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ የሚያስችሉ ሥራዎች እየተሠሩ መሆኑን ጠቁመው፣ በግብርና ኢኒሼቲቮች የእንስሳት ሀብቶቻችን ወደመጠቀም ተሸጋግረናል ብለዋል።
‎የገጠር ትራንስፎርሜሽን ላይ ትኩረት ተደርጎ እየተደረገ መሆኑን የጠቀሱት አቶ አሻድሊ፣ በዚህም የግብርና ምርታማነት ከመጨመር ባለፈ የገጠሩን ማኅበረሰብ ሕይወት ለማሻሻል እየተሠራ መሆኑን ገልጸዋል።
‎ክልሉ ለሩዝ ምርት አመቺ መሆኑን የተናገሩት አሻድሊ፣ ለዚህም በምርት ዘመኑ የተሠራው ሥራ ትልቅ ማሣያ በመሆኑ በቀጣይ ሩዝን ጨምሮ የቅባት እህሎችን በስፋት ለማምረት መሥራት ይገባል ብለዋል።
‎የክልሉ ግብርና ቢሮ ኃላፊ አቶ ባበክር ኻሊፋ፣ በ2017/18 የምርት ዘመን ከ1 ነጥብ 5 ሚሊዮን ሄክታር በላይ ማሣ በዘር መሸፈኑን ገልጸው፣ 56 ሚሊዮን ኩንታል ምርት እንደሚሰበሰብ ጠቁመዋል።
‎በምርት ዘመኑ የታረሰው መሬት ካለፈው የምርት ወቅት ጋር ሲነጻጸር የ400 ሺህ ሄክታር መሬት ዕድገት አሳይቷል ብለዋል።
‎በምርት ዘመኑ 355 ሺህ 335 ሄክታር መሬቱ በክላስተር መልማቱንም አቶ ባበክር አንስተዋል።
‎የባምባሲ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ አብዱልዋህድ አዙቤር፣ በወረዳው በግብርናው ዘርፍ አበረታች ሥራ እየተሠራ መሆኑን ጠቁመው፣ በተያዘው የምርት ዘመን 8 ነጥብ 1 ሚሊዮን ኩንታል ምርት ይጠበቃል ብለዋል።
‎በወረዳው መሣቸውን በክላስተር ያለሙ አርሶ አደሮች በበኩላቸው፣ ከስልጠና ጀምሮ ተከታታይ ድጋፍና ክትትል ማግኘታቸው ውጤታማ እንዳደረጋቸው ተናግረው፣ በቀጣይ የተሻለ ለመሥራት ዕቅድ እንዳላቸውም ተናግረዋል።

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *